መዝሙረ ዳዊት

" እግዚአብሔር አምላኩ የሆነለት ሕዝብ ብፁዕ ነው። " መዝ 32 ፦ 12

Saturday, December 11, 2010

ያማል!

ያማል!

እና እንደነገርኩሽ ...
የሚወዱትን ሰው ቀጥሮ እንደመጠበቅ
የነፍሰ-ጡርን ሞት አይቶ እንደመሳቀቅ
ባልታሰበ ናዳ ተመትቶ እንደመድቀቅ
ከተስፋ ጉልላት ተገፍቶ እንደመውደቅ
ታምር በበዛባት በዚች ቧልተኛ ዓለም
ከዚህ የበለጠ ምንም ሕመም የለም።
***
አውቶቡሱ ያማል
ሚኒባሱ ያማል
ላዳ ታክሲው ያማል
የማይጎድል የሰው ጎርፍ ... ደራሽ ማዕበሉ
         ... የዕንባ ቅጥልጥሉ
ምን ብዬ ልንገርሽ ... ያማል ይኼ ሁሉ።
***

Friday, November 12, 2010

ሌላ ሞክሪ

ሌላ ሞክሪ

ካ'ንጀትሽ ጠልተሽኝ 
       ' አፈር ድሜ  ብላ '
ብለሽ ብትሰድቢኝም
አይሞቅ አይበርደኝም 
አፈርሽ እንደሆን ... አያሳድፈኝም
        ቢሆን ነው ካባዬ
        ድርብርብ ቀሚሴ
        ተጨማሪ ልብሴ

መላ በሉኝ

መላ በሉኝ

ሽፍን ድብቅ ያለ ... እምቅ እጭቅ ያለ
መፍቻ 'ሚሆን ቀመር ... እንደ ስሌት ነገር
ያጣሁለት መላ ... ጥቂት እንዲላላ
************************
ውስብስብ ' ቋጠሮ '
አለመጠን ከ ... ሮ
*************************
ልቤን ልብ ነሳው ... አደብ አቅል አሳጣው
መፈንዳቱ አሰጋኝ ... ልፈታው ቸገረኝ
እንዳሻህ ለማለት ... ትዕግስቱ ባይኖረኝ
**************************
ድሮውንስ ቢሆን የምን ቋጠሮ አለ?
አድናቂ የሌለው በሕሊና ያለ
ስዕል ነው! ... ንድፍ ነው!
ብዬ ላሾፍበት ... አሳር አየሁበት።

Jack Bauar's Final Hour ... What A show!!!

Thursday, October 14, 2010

መለያየት ሞት ነው!

 መለያየት ሞት ነው!

አቤት አቤት እኛ
እኛ ...
ተጎዳን ክፉኛ
እንዲህ ተለያይተን
እጅግ ተነጣጥለን
ስንገኝ ለብቻ
ድህነት ... በሽታ ... ወጡብን ዘመቻ።
**************************
ለዘመቻ አፀፋ
ፍቅራችን ቢሰፋ
ብንሆን በህብረት
በፍቅር ባንድነት
ዘማቹ ባፈረ
ጉዳት ብሎ ነገር ... ድ ... ሮ ... ጥንት በቀረ።

Monday, September 20, 2010

የመስጠትና የመቀበል ሥሌት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

የመስጠትና የመቀበል ሥሌት

የሰውን ልጅ የኑሮ ዑደት ፤ ሚዛን በመጠበቅ ረገድ የመስጠትና የመቀበልን ያህል ሚና ያለው አንዳች ነገር ፈልጎ ማግኘት እጅጉን አዳጋች ነው። የሥነ-ፍጥረትን አሰራር ፣ አካሄድ ፣ እና አኗኗር በማስተዋል ለተመለከተ ሰው ፤ የዚህ ዓለም ፈጣሪና መጋቢ እግዚአብሔር አምላክ ፤ ዓለሙን በዚህ የመስጠትና የመቀበል ሥሌት እንዳፀናው ለመረዳት አይቸግርም ፤ ለአብነት እንኳ  የሰውን ልጅ የአተነፋፈስ ሥርዓት ብንመለከት ፤ ወደ ውስጥ የምናስገባውን ኦክስጅን ለመቀበል ምንም ያገለገለና የተቃጠለ ብንለው ካርቦን ዳይ ኦክሳይድን መስጠታችን ( ማስወጣታችን ) ድርድር የማያስፈልገው ነው ፤ ባንጻሩም ዕፅዋትና አዝርዕትም ቢሆኑ ፤ በፋንታቸው ምግባቸውን ለማዘጋጀት እንደ አንድ ግብዓት የሚያስፈልጋቸውን ካርቦን ዳይ ኦክሳይድ ለመቀበል ኦክስጅንን መስጠት ይኖርባቸዋል። ... ይኸስ ባይሆን ኖሮ ሁሉን ሊያደርግ የሚቻለው ፈጣሪ ፤ በየጊዜው ፦ በየዘመኑ ለሚኖሩ ሰዎች እና ዕፅዋት እንደ ልካቸው ( ብዛታቸው ) የሚያስፈልጋቸውን ፤ ለዚህን ያህል ሰው ይህንን ያህል ኦክስጅን ፣ ይህንንም ያህል ካርቦን ዳይ ኦክሳይድ ፤ ለዚህን ያህል ዕፅዋትም ... እያለ እየሰፈረ እና እየለካ ባዘጋጀ ነበር ፤ ነገር ግን ፈቃዱ ለአንዱ መኖር የሌላውን ህልውና ግድ የሚል ፤ አንዱ እንዲቀበል ለሌላው መስጠትን ቅድመ ሁኔታ ያደረገ ፤ አንዱ ለሌላው ፣ ሌላውም በሌላው ላይ ያለውን ተደጋግፎት የሚጠይቅ ፤ ... ነው።

በቅዱስ መጽሐፍ ፤ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመስጠትንና የመቀበልን ሥሌት በተለያዩ ሀገራት ለተለያዩ ሰዎች እንዳስተማረና ይኼውም ትምህርቱ የዘለቃቸውና የተረዳቸው የተጠቀሙበትም በፊልጵስዩስ የነበሩት ሰዎች ብቻ እንደነበሩ ተጠቅሶ አለ። " ከእናንተ ብቻ በቀር ሌላ ቤተክርስቲያን በመስጠትም ቢሆን በመቀበል ከእኔ ጋር እንዳልተባበሩ እናንተ ታውቃላችሁ " ፊሊ 4 ፦ 15 .... እኒህ በጥንቷ ግሪክ ሰሜናዊ ጫፍ ፤ በመቄዶንያ አውራጃ ትገኝ በነበረችው  ፊልጵስዩስ የነበሩ ሰዎች ይህን የመሰለውን ምስክርነት ከታላቁ ሐዋርያ ያገኙት ፤ ሐዋርያው በሮም ሀገር የቁም እስረኛ በነበረበት ወቅት ልከውለት ሥለነበር አስተዋፅዖ ምክንያት ነው። ... ለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከተላከለት አስተዋፅዖ ላገኘው ጥቅም ምስጋና ፤ ይኸውም አስተዋፅዖዋቸው እንዳይቋረጥበት ሰግቶ ይህንን ተናገረን? ... እንዲያውም! ... ይልቁንስ ከበጎ ሀሳባቸው የተነሳ ሁሉ ካለው አምላክ ዘንድ በረከትን እንደሚያገኙ አስቦ ተናገራቸው እንጅ ፤ ይኼውም " ይህንም የማነሣሣው ስጦታችሁን ፈልጌ አይደለም ፤ በእናንተ ላይ የጽድቅ ፍሬ ይበዛ ዘንድ ፈልጌ ነው እንጅ " ፊል 4 ፦ 17 ባለው ይታወቃል። ... በዚህ ዘመንም ሰዎች በተለያዬ ሁኔታና መንገድ በተለያዩ ምክንያቶች ተነሳስተውና ተገፋፍተው አስተዋፅዖ ያደርጋሉ። ... ለመሆኑ ከሚሰጡት መካከል ... ስንቶቹ  ደጅ ተጠንተው ሰጡ? ... ስንቶቹስ ይህን አደረጉ ፤ ይህንን ደግሞ ሰጡ ፤ አጨብጭቡላቸው ፤ እልል በሉላቸው መባልን ሽተውና ስማቸው በአደባባይ እንዲጠራ ፈልገው ሰጡ? ... ስንቶቹስ ባለማስተዋልና በክፉ ብልጣብልጥነት ፤ ዘርዝረው የበተኗት አንድ ብር አንድ ሽህ እንድትወልድ ሰጡ? ... ስንቶቹስ እንደ ፊልጵስዩስ ሰዎች ባለ መልካምነት ፤ የሚሰጡት ገንዘብ እግዚአብሔርን ሊደጉመው ፤ የሚያመጡት እጣን ከመዐዛው መልካምነት የተነሳ ሊያሸተው ፤ የሚያገቡት ጧፍም ጨለማውን ሊያርቅለት ሳይሆን ፤ የሰጡትን ከሰጡበት በጎ ኅሊና ( ሀሳብ ) የተነሳ የእግዚአብሔርን በረከት ሽተው ሰጡ? ... ቤት ይቁጠራቸው። ... የመስጠትና የመቀበል ሥሌቱ የገባቸው የፊልጵስዩስ ሰዎችስ ' እኛ በጫና ያይደለ በውድ ያለንን ደስ እያለን እንሰጣለን ፤ አንተ ደግሞ ለእኛ ምን ፤ መቼ እንደሚያስፈልገን ታውቃለህ ፤ በጊዜህም ታደርግልናለህ ' በሚል እምነት ሰጡ።

Wednesday, September 1, 2010

እንዲህም ብሎ ትዕግሰት እቴ i

እንዲህም ብሎ ትዕግሰት እቴ i

 ተቆርጦ ቀርቶ ... መሃል ገብቶ
ተከቦ አይቼው ... መውጫ አጥቶ
ታገስኩኝ ይላል ... አፉን ሞልቶ።

Monday, August 30, 2010

ወመኑ ዘየኃሥሶ ጥበበ ለዝ ዓለም? 1 ቆሮ 1፦20-23

የዚህን ዓለም ጥበብ የሚሻው ማነው?

በእግዚአብሔር በጎ ፈቃድ የክርስቶስ ኢየሱስ የመንግስቱ ወራሾች እንሆን ዘንድ ከተጠራን ከእኛ ከወንድሞቻችሁና ከእኅቶቻችሁ ፤

የጥበብን ፋና ስለመግዛት ፤ የድንቁርናን ጨለማ ስለማራቅ ፤ ራስን ፣ ቤተሰብንና ሀገርን በእውቀትና በሀብት ስለማሳደግ ምክንያት በየትምህርት ተቋማቱ ሆናችሁ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥም ለምትጠሩ ፤ ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና ሰላም ለእናንተ ይሁን።

Tuesday, August 24, 2010

እናንተን ... " የሴት ልጅ " አሏችሁ?

እናንተን ... " የሴት ልጅ "  አሏችሁ?

' የሴት ልጅ ' ተብላችሁ
በእጅጉ የከፋችሁ
እጃችሁን ... እስቲ ልያችሁ
/ በቃ! ... በቃ! ... በጣም በዛችሁ /
ይኼ መስፈርት ያሻዋል ... ልብ ብላችሁ አድምጡ
ያገባናልም ስትሉ ... ቶሎ ወደ ዳር ውጡ።
*****************************
በመጀመሪያ ...
በኑሮ ትግል ያልተረታ
በውሽንፍሩ ያልተፈታ
የእናቱ ወኔ ያለው 
እርሱ ካለ እንየው
የለም?
******************************
በመቀጠል ...
ማጣት ያላሟጠጠው
' ልጄ ... ልጄ ... ' የሚያስብለው
ፍቅሯ ያለው
እርሱም ካለ እንየው
እርሱም የለም? ...
*******************************
እህ ...
ታዲያ ለምን ከፋችሁ?
እናንተ ' የሴት ልጅ ' አይደላችሁ።

Thursday, August 19, 2010

ዝም ያለ ... ዝም! አለ

ዝም ያለ ... ዝም! አለ

' ዝም
አይነቅዝም ' ሲሉት
... ዝም ሲል
' ዝምታ 
ወርቅ ነው ' ሲሉት 
... ዝም ሲል
' ዝም ባለ አፍ 
ዝምብ አይገባበትም ' ሲሉት
... ዝም ሲል
ዝም! አረጉት አሉ
ወደህ በገባህ እያሉ።

10/01/98
ዲላ

መወለድ ቋንቋ ነው።

መወለድ ቋንቋ ነው።

መለያየት ነግሶ ... ብልጥነት አይሎ
መቻቻል ተረስቶ ... ሞኝነት ተብሎ
                    ' ባዳማ ባዳ ነው ' ... ተዘውትሮ በጣም
                    ' ዘመዴ ዘመዴ ' ... ማለት አያዋጣም።
ልብ ተራርቆ ... መግባባት ከታጣ
ዘመድም ባዳ ነው ... መላቅጡን ያጣ
                     ዘር መቁጠር ግን ቀርቶ ... መመቻቸት ቢኖር
                     መወለድ ቋንቋ ነው ... አይደለም ቁምነገር።


18/02/98
አዋሳ

ደብረ ታቦር

Wednesday, August 18, 2010

የፈጣሪን መኖር እንዴት ማወቅ ይቻላል?

የፈጣሪን መኖር እንዴት ማወቅ ይቻላል?

ሰው በልዩ ልዩ ተፅዕኖ ምክንያት በራሱ ፈቃድና ውሳኔ ካልተወው በቀር ፤ የፈጣሪን ሀልዎት ( መኖር ) ፈልጎና መርምሮ የሚያውቅበት እውቀትና ችሎታ ፤ ደግና ክፉን ለመለየት የሚያስችለው ሕገ - ልቦና ( የሞራል ሕግ ) በተፈጥሮ እንደተሰጠው የታመነ ነው። በሞራል ሕግ - በምርምር የፈጣሪን መኖር ማወቅ አይቻልም በማለት በነፃ ፈቃዳቸው በድፍረት ወስነው የሃይማኖትን ነገር ፈፅሞ እንዳያስቡ የኅሊናቸውን በር የዘጉትን ሰዎች ወደጎን ትተን ፤ በመጀመሪያ ሥነ-ፍጥረትን ቀጥሎም ሰብአዊውን ፍጡር ፤ ሰውን ፦ በተለየ መልኩ በመመርመር እንዴት የፈጣሪን ሀልወት ማወቅና ፤ መረዳት እንደሚቻል እነሆ ፦

የሥነ-ፍጥረትን ገጽታና ሁኔታ ፤ አሰራርና አካሄድ በመመልከት የማያደንቅ ሰብአዊ ፍጡር አይኖርም። በአጠቃላይ የሥነ-ፍጥረትን ውበት ፣ የአፈጣጠሩን ሥርዓት ፣ በቀን የፀሐይ ብርሃንና ሙቀት፣ በሌሊት የጨረቃዋን ድምቀት ፀጥታና ሰላም በሰፈነበት ሁኔታ በተረጋጋ ኅሊና ለሚያስተውለው ሁሉ የመገረም ስሜት ያድርበታል። ከበላያችን ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የተዘረጋው መጨረሻ የሌለው የሰማዩ ስፋትና ጥልቀት ፤ በሌሊት የሚያብረቀርቁት ከዋክብት ብዛት ፤ የአቀማመጣቸውና የእንቅስቃሴያቸው ሥርዓት ፣ የዘመናት መፈራረቅና ሌሎችም የተፈጥሮ ክስተቶች እጅግ ያስደንቃሉ። በተለይም በምድራችን ዙሪያ የሚገኙት ሕይወት ያላቸው ለምለም እፅዋት ፣ በእግር የሚንቀሳቀሱ እንስሳት ፣ በክንፍ የሚበሩ አእዋፍና የሌሎችም አፈጣጠር በየወገናቸው ሲጠና ይልቁንም የሰዎች ልጆች ረቂቅ ተፈጥሮ ሲታይ በአጠቃላይ የሥነ-ሕይወት ክስተት ጉዳይ ሲመረመር አስተዋይ ኅሊና ያለውን ሁሉ ያስጨንቃል ፤ ያስጠብባል።

Monday, August 16, 2010

መሸ? ፤ ነጋ?

መሸ? ፤ ነጋ?

ልጆቹ ... ልጆቹ
እኒያ ጨቅላዎቹ
ኩኩሉ አኩኩሉ ... እየተባባሉ
ምሽትና ሌቱን ... ቶሎ ያነጋሉ።
ወዲያው ደግሞ ሲያድጉ ... ኩኩን ሲዘነጉ
        ...ጭንቅ ይላቸዋል ...
የቀኑ አመሻሸት ፤ የሌቱ አነጋጉ።


29/10/97
ዲላ

Wednesday, August 11, 2010

ከማን ታንሳላችሁ? iii

ከማን ታንሳላችሁ? iii

እነኛ ...
ዛሬ ሊያወጉ
አውግተውም ሊያዋጉ
ተዋጉ።
እናንተም ... 
ነገ እንድታወጉ
አውግታችሁም እንድታዋጉ
ጠብቃችሁ ተዋጉ i i i


09/01/98
ዲላ
( በዘር ምክንያት ለምትዋጉት )

ብልጠት ወይስ ሞኝነት?

ብልጠት ወይስ ሞኝነት?

የምኞት ድንበር ሲጣስ
          ራስ
ሁሉን አድራጊ ንጉስ
         ዐይን
አሁንም አሁንም የሚያይ
ሽቅብ ወደላይ ወደላይ።
****************
ሽቅቡን መውጣት መጀመር
     የማይገፋ ነገር
ድንገት ከጫፍ  ቢደረስ
ያሰቡት ከልብ አይደርስ።
****************
ይህን ጊዜ
ትካዜ።
***************
ተመልሶ ለመውረድ
አልቦ መንገድ
መንገዱ ቢኖር
አቅምና መላ ችግር።
**************
እንዲህ ... ውጥንቅጡ የወጣ ጊዜና
'እርሱ ... እግዚአብሔር ነውና
ያሻውን ፤ የፈቀደውን ... ያድርግ ' ማለት
ብልጠት ወይስ ሞኝነት?


22/09/2001
አ.አ

Friday, August 6, 2010

" የበላም ለራሱ ...የጾመም ለራሱ " ?

" የበላም ለራሱ ...የጾመም ለራሱ " ?

የበላ ... ለራሱ በላ
* * * * * * *
የበላ ... ሆዱ ሞላ
ሆዱ የሞላ ... ለስጋ ፈቃዱ አደላ
ለስጋ ፈቃዱ ያደላ ... ለነፍሱ ሆነ ተላላ
ለነፍሱ የሆነ ተላላ ... ከፈጣሪው ተጣላ
ከፈጣሪው የተጣላ ... እርሱ በሲኦል እሳት ሊበላ
               ጦሡ ተረፈ ለሌላ።
                 * * * * * * *
የጾመ ... ለራሱ ጾመ
* * * * * * *
የጾመ ... ስጋው ደከመ
በስጋው የደከመ ... የነፍሱን ፈቃድ ፈፀመ
የነፍሱን ፈቃድ የፈፀመ ... በፈጣሪው ፊት ቆመ
በፈጣሪው ፊት የቆመ ... ስለምግባሩ በመልካም ሁሉ ተሾመ
          ስለ'ርሱም ... ሌላው ካገኘው ደዌ ታከመ።

30/11/2002
Tromso, Norway

Thursday, August 5, 2010

ሊያሳስበን የሚገባ ሌላ ጉዳይ ...


በስመ ሥላሴ አሜን።
የቤታችንን ችግር አስመልክቶ  የተለያዩ ነገሮችን  በተለያየ መንገድ  ከተቆርቃሪዎችም ሆነ ግድ ከሌላቸው ወገኖች ብዙ ሰምተናል ... ከአንዳንዶቹም ጋር አብረን መክረናል ... ችግር ፈጠሩ ያልናቸውን አካላትንም  ኮንነናል ፤ ወቅሰናል ... መፍትሔ ስለምንለውም ነገር ብዙ ብለናል ... ነገር ግን አሁን በፊታችን ተገልጦ የምንጯጯህበት ይህ የቤተ-ክህነት ችግር እኛ ባሰብነውም ይሁን በሌላ ዘዴ ቢፈታ ወይም የተፈታ ቢመስል  እንኳ ትቶት ሊያልፈው ስለተዘጋጀው ጠባሳ ስንቶቻችን እናውቃለን?
በምንኖርባት በዚች አለም መሪዎች በተመሪዎች ላይ ቀንበር ሲያከብዱ ፤ ግፍን ሲያደርጉ ተመሪዎቹ በመሪዎቹ ላይ መነሳታቸው ፤ በተወሰኑትም መስዋዕትነት ሌሎቹ ነፃነታቸውን እንደሚያገኙ ታሪክ ምስክር ይሆናል ፤ ... ነገር ግን ይህን መሰሉ ክስተት የሚሰራው በአለም ነው! ... ምንም እንኳ እኛ ምዕመናን በአለም ውስጥ የምንኖር ቢሆንም ... በእግዚአብሔር ቤት አካሔዱ የተለየ ነው ... ሊለይም ይገባዋል ... ምክንያቱም አልቻለን እያለ ቢቸግረን ነው እንጅ ልንፈጽመው የምንወደው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ነውና ... ሀገራችንም በሰማይ ነውና ... በመሆኑም የቤተ-ክህነት ችግር መፍትሔ በምስኪን ምዕመናን መስዋዕትነት ወይም ዋጋ ሊታሰብ አይገባውም  ... ለዚያውም መስዋዕት ስለሆኑበት ነገር በውል በማይረዱበት ሁኔታ ...

Friday, July 30, 2010

" እግዚአብሔር የሚወደውን መልካሙንና እውነቱን ፍፁሙንም መርምሩ " ሮሜ 12 ፦ 2

" እግዚአብሔር የሚወደውን መልካሙንና እውነቱን ፍፁሙንም መርምሩ " ሮሜ 12 ፦ 2

በስመ ሥላሴ አሜን።

ሰላመ እግዚአብሔር ይብዛላችሁ።

" እያንዳንዳችን ...
  ቤታችንን ..
  ብንጠርግ ... ብናፀዳ
  አዲስ አበባችን ... ምን ያህል በፀዳ "
*  * * * * * * * * * * *
የማይመስል ነገር ... የማይሆን ግርግር
             ...  የቆሻሻ ክምር ...
'ራሱ ቆሽሾ ሌላውን ሊያቆሽሽ ባሰፈሰፈ አገር።

ይህችን ግጥም ቢጤ ፦ በአንድ ወቅት በመዲናችን በአዲስ አበባ እና በአንዳንድ የክፍለሃገር ከተሞች ሰሞነኛ አጀንዳ ሆኖ ለሰነበተና ለቅፅበት ታይቶ ለጠፋ የፅዳት ዘመቻ ነበር የሞነጫጨርኳት ...

በወቅቱ የዘመቻ ባህሪይ ከሆነ ትኩሳትና ስሜታዊነት የተነሳ የከተሞችን ገፅታ በመቀየር ሒደት የተለያዩ እና ሊጠቀሱ የሚችሉ ተግባራት ሲሰሩ እንደነበረ የብዙዎቻችን ትውስታ ነው። ... የሆኖ ሆኖ ወደ ዘመቻ የተገባው የህዝቡን አመለካከት በማሳደግ በኩል በቂ ስራ ሳይሰራ በመሆኑ የተጠበቀው አዲስ አበባን ፅዱና አረንጓዴ የማድረግ ግብ ከፍፃሜ ሳይደርስ ... የአንድ ሰሞን ዘመቻ ብቻ ሆኖ ቀርቷል። ለዚህም በአዲስ አበባ ባምቢስ እና መገናኛ ድልድይ አካባቢየሚገኙ ቦታዎችን ለአብነት ማንሳት ይቻላል ... አምረውና ተውበው ለህዝብ አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን አውርተን ሳንጨርስ ወደቀደመ የቆሻሻ መነኻሪያነታቸው ተመልሰዋልና ... እንዲህም ማለቴ በጊዜው የነበረውን መነሳሳት ፤ የዚህንም መነሳሳት ግምባር ቀደም ተዋናይ ፦ የአርቲስት ጋሽ አበራ ሞላን ዋጋ ለማሳነስ ( ቸርችል ቪውን የመሰሉ ምሳሌ የሆኑና ይበል የሚያሰኙ ስራዎች የዚህ መነሳሳት እሳቤ ውጤቶች ናቸውና )  ሳይሆን የህዝቡ የአመለካከት ለውጥ ዘመቻውን ሊቀድመው ይገባ ነበር ለማለት ነው። ...

Thursday, July 22, 2010

ስብሐት ይሁን

ስብሐት ይሁን

ለ ... ጭንቀት
ለ ... ርሀብና ለ ... ጥማት
ለ ... ድካም
ለ ... ስቃይና ለ ... ህማም
ብቻ ...
ቀድሞ ለ ... 'ሚሆን
ችጋር ...
ስብሐት ይሁን።
እንዲያ ባይሆን ሲጀመር
ደስታ ፤ ሐሴት ... 'ሚባል ነገር
እንዴት ይገባን ነበር?



21/12/98
ይርጋለም

Wednesday, July 21, 2010

" በእምነት ስላልተዋሃደ ... አልጠቀማቸውም " ዕብ 4፦2

" በእምነት ስላልተዋሃደ ... አልጠቀማቸውም " ዕብ 4፦2

በስመ ሥላሴ አሜን።

በእግዚአብሔር በጎ ፈቃድ ከእኔ ከወንድማችሁ ፦ የክርስቶስ ኢየሱስ የመንግስቱ ወራሾች ትሆኑ ዘንድ ለተጠራችሁ ለናንተ ፦ ከእግዚአብሔር ከአባታችን ፤ ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና ሰላም ለእናንተ ይሁን።
ወንድሞች ሆይ ፦ የነፍሳችንን ድኅነት ፤ የልጅነትን ክብር ፤ ተስፋ ስለማድረግ ምክንያት በቤተክርስቲያን ጥላ ስር በእምነት የምንኖር ነንና እራሳችንን ከእግዚአብሔር ቤት ሕግና ሥርዓት በታች እናስገዛለን ፤ ታዲያ ምንም እንኳን በልቦናችን ያለው ይህ የእግዚአብሔር ሕግ መልካም ቢሆንም (ሮሜ 7 ፦ 22) ከሥጋችን ደካማነት ፣ ከዲያቢሎስም ውጊያ የተነሳ የኃጢአትን ሕግ እንመለከታለን። እንዲህም ስለሆነ እባብ ሔዋንን በተንኮሉ እንዳሳታት ለሥጋ በመድከማችን ምክንያት አሳባችንና ፈቃዳችን ከክርስቶስ የዋህነትና ንፅህና ምናልባት እንዳይለወጥ ብዬ እሰጋለሁ። ... ወዲህም ደግሞ " እግዚአብሔር የሚወዱትን ምርጦቹን በበጎ ምግባር ሁሉ እንደሚረዳቸው እናውቃለን " (ሮሜ 8 ፦ 28) ስለተባለው የተስፋ ቃል ከስጋቴ አርፋለሁ ... ቢሆንም ግና አሁንም መልሼ እሰጋለሁ ... እግዚአብሔርን ከሚወዱት ከምርጦቹ መካከል አንሆን ይሆን ብዬ ... ምክንያቱስ ፦ እርሱን የሚወዱ ፍለጋውን ይከተላሉ ተብሏልና ... ታዲያ ስንቶቻችን ጎዳናውን ተከትለናል? ... እግዚአብሔርን መውደዳችንስ ወዴት አለ? ... እንዴትስ እየገለፅነው ነው? ...

Tuesday, July 20, 2010

ያልታደለችዋ ዛፍ

ያልታደለችዋ ዛፍ

ባንድ ወቅት የአንድ ዛፍ
ግንዱ ከቅርንጫፍ
ቅርንጫፍም ባቅሙ ከሌላ ቅርንጫፍ
ተጣሉ ይባላል ፈልገው ትርፋ ትርፍ።

ታዲያ በዚህ ነገር ስሩ እጅግ አዝኖ
ሊሸመግል ገባ በመካከል ሆኖ

ከዚያም ሽማግሌው ሁሉንም ቃኘና
እርቁን አስጀመረ እንደዚህ አለና
ስሙ አካላቶቼ ነገሬን አድምጡ
ሕይወታችን ሆኗል ከድጥ ወደማጡ።
ምንም እንኳ ምግቡ ብዙ ቢትረፈረፍ
ተፈጥሮ ቢያድለን ሁሉን ነገር በገፍ
ያው እንደምታውቁት እኔ አባታችሁ
በጎርፍ በፀሀዩ ደካማ ሆኛለሁ።
እንዲያም እንኳ ቢሆን እንደምንም ብዬ
ቁሩንም ጎርፉንም ንዳዱንም ችዬ
ለኑሮ የሚሆን ምግብ ፈላልጌ
እየላክሁላችሁ በግንድ አድርጌ
እየኖርን ነበር በሰላም ተዋደን
ችግሩን ስቃዩን በአንድነት ችለን።
ሰሞኑን ግን እኔን አልጥምህ ብሎኛል
ጠባችሁ ከባብዶ ገዛዝፎ ታይቶኛል።

በማለት አቅንቶ ግንዱን ተመልክቶ
የብዙ ቅርንጫፍ ክስን ሁሉ አይቶ
እንዲህ ሲል ወቀሰው በሀዘን ተጎድቶ

Saturday, July 17, 2010

ተረት ተረት

ተረት ተረት

*********
ድ***ሮ***በጥንት ጊዜ ነው አሉ
የዱር አራዊት የተባሉ
በ***ሙ***ሉ
በየወገን በየወገናቸው
በየጫካ በየስርቻቸው
አስተዳዳሪ፤
መሪ፤
የሚሉት ኖሯቸው
ይኖሩ ነበር ደልቷቸው
***ተመችቷቸው።
*************
ከዚያም ሲኖሩ ፣ ሲኖሩ ፣ ሲኖሩ
**************
ከእለታት በአንድ ቀን
አንበሳ የሚሉት ወገን
ከነበረበት ፤ ካለበት ... እምቡር ብሎ ወጥቶ
አራዊቱን ሁሉ በክርኑ እጅ ... አሰጥቶ
ራሱ ሿሚ
እሱው ተሿሚ
ሆኖ አስተዳዳሪ ... የዱር አራዊቱ ሁሉ መሪ
***************
የራሱን የኑሮ ድሎት
የራሱን መንደር ምቹነት
የናንተም ነው እያለ ... እየለፈፈ
ደንቁሮ እያደነቆረ ... ዘመናትን አሳለፈ።
****************
ታዲያ እነርሱም ...
ብ ... ዙ ... በጣም ብዙ ግፍ እየቆጠሩ
ባንበሳው አገዛዝ እየተማረሩ
ብዙ ዘመን ኖሩ።
***************
ጥያቁም ሲያነሱ
... ስለሚደቆሱ
ጨከን ... ጨከን ያሉ
ካያ አንበሳ ይርቃሉ
በሌላ ጫካ ፤ በሌላ ስርቻ
... የስደትን ኑሮ ይገፋሉ።
ለመጨከን ያልታደሉ
በየወገናቸው ያንሾካሹካሉ
ያንሾካሹካሉ ... ያንሾካሹካሉ
ድንገት ጮክ ሲሉ ... ይኮረኮማሉ
ተመልሰው ያንሾካሹካሉ
... ይደቆሳሉ።
ያንሾካሹካሉ ፤ ያንሾካሹካሉ
... ያንሾካሹካሉ ...



02/05/98
አ.አ.

Wednesday, July 7, 2010

አንተ 'ወንበር' ... እባክህ ተናገር

አንተ 'ወንበር' ... እባክህ ተናገር

አንተ የኛ ቤት ... ትልቅ 'ወንበር'
እስኪ ተጠየቅ ... በል ተናገር
* * *
አንተን የነካህ ... በ...ሙ...ሉ
ተቀያይሮና ... ተለዋውጦ አመሉ
ጨክን ጨክን ... የሚለዉን
ፍርድ አጓድል ... ያሰኘውን
ንገረን እስኪ ... በሽታውን
* * *
በበፊቱ ወንበር ... መቆርቆር
የኖረው ሁሉ ... ሲያማርር
ቀን ሲወጣ ... እድል ሲያምር
ሲፈናጠጥ ... ያንተን መንበር
የቀየረውን ... በል ተናገር
* * *
ሞገስህ ነው? ድሎትህ?
ሙቀትህ ነው? ቁመትህ?
እባክህ አንተ 'ወንበር'
ጨንቆናልና ተናገር።


12/01/98
ዲላ

Tuesday, June 29, 2010

የሕሊና ሕግ

የሕሊና ሕግ

የንስሐ አባቴ ልጆቻቸውን ሰብስበው የማስተማር በጎ ልማድ አላቸው ፤ ታዲያ ተሰባስበን በምንማማርበት በአንድ ወቅት ፤ እንወያይበት ዘንድ አንድ ርዕስ አንስተው ነበር " የአንድ ክርስቲያን ሥነ-ምግባር መለኪያው ምንድን ነው? " የሚል ... በወቅቱም ከአንድ ወንድሜ እና ከሦስት እህቶቼ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ብዙ ከተወያየን በኋላ የንስሐ አባታችን የሰጡት ማጠቃለያ በተለይም ሕሊናን የተመለከተው በአእምሮዬ ሲመላለስ የከረመ ነበርና ብዕሬን አነሳሁ።

እኔ እና ወንድሜ

እኔ እና ወንድሜ

የአባቴ እና የአባቱ
የጥንስሳቸው መሰረቱ
ሐረጋቸው ሲመነዘር
አንድ ተብሎ ሲቆጠር
ሀሳባቸውና ፈቃዳቸው
የአኗኗር ቅኝታቸው
ለየቅል የተገነባ
ላይገናኝ ቃል የተጋባ

ነበሩ...አሉ ሁለቱም
የተራራቁ በጣሙን

ወንዘኞችና ጎጠኞች
ለብቻየ የሚሉ ምቀኞች
ልዩነትን እንደ ልዩነት
ያልታደሉ ለመመልከት
ያልነበረውን አንድነት
ያልነበረውን ሕብረት
እንደነበረ የሰበኩ

ነበሩ...ይላሉ የታዘቡ
የትዝብት መጽሐፋቸውን ሲያነቡ